የየካቲት 6 ሥንክሳር
Автор: kesisephrem
Загружено: 2026-02-12
Просмотров: 90
Описание:
ስንክሳር ዘወርኀ የካቲት 6
አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም የካቲት ስድስት በዚች ቀን የዓለሙ ሁሉ መምህር የሆነ የሮሜ ሀገር ሊቀ ጳጳሳት የከበረ አባት አቡሊዲስ ሥጋው ከባሕርየወጣበት ነው ።
ይህም የከበረ በእውቀቱም ፍጹም የሆነ ሰው ነው ከአባት አውክዮስም በኋላ ለሮም ሀገር ሊቀ ጳጳሳት ይሆን ዘንድ መንፈስቅዱስ መረጠው ይህም የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት ከላድያኑ በተሾመባት በመጀመሪያ ዓመት ነው ሕዝቡንም ከአረማውያን ጠባይ የሚጠብቃቸው የሚያስተምራቸውና በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሃይማኖት የሞያጸናቸው ሆነ
በከሀዲውም ንጉሥ በከላድያኖስ ዘንድ ዜናው ተሰማ ይህንንም የከበረ አቡሊዲስን ይዞ በብዙ ግርፋትና ድብደባ አሠቃየው ማሠቃየቱንም በሰለቸ ጊዜ በእግሮቹ ውስጥ ታላቅ ደንጊያ አሥሮ ከጥልቅ ባሕር የካቲት አምስት ቀን አሰጠመው ። ማግሥትም ሲሆን የካቲት ስድስት በዛሬዋ ቀን የዚህ አባት ሥጋው በውኃ ላይ ተንሳፎ ተገኘ ደንጊያውም በእግሮቹ ውስጥ እንደታሠረ ነበር አንድ ምእመን ሰው ወስዶ በርሱ ዘንድ አኖረው በከበሩ ልብሶችም ገንዞ ሠወረው ። ወሬውም በሮሜ አገሮች ሁሉ ተሰማ ንጉሡም ሊአቃጥለው ፈልጎት ነበር ግን አላገኘውም ያ ሰው ሠውሮታልና ።
ይህም የከበረ አባት ስለ ቀናች ሃይማኖት ብዙ ድርሳናትን ደርሶአል ከእርሳቸውም ስለ አካላዊ ቃል ሰው መሆንና ከኃጢአት በቀር በሥራው ሁሉ አንድ ባሕርይ ሰለ መሆኑ የደረሰው አለ ። ዳግመኛም እግዚአብሔር የሚወደውን ስለ መሥራት የደረሳቸው ተግሣጻትና ትምህርቶች አሉ ስለ ቤተ ክርስቲያንም ሕግ ሠላሳ ስምንት መመሪያዎችን ሠርቷል እሊህም በሁሉ አብያተ ክርስቲያን ይገኛሉ ።
ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን እኛንም በዚህ አባት ጸሎት ይማረን በረከቱም ከእኛ ጋርትኑር ለዘላለሙ አሜን ።
ቅድስት አትናስያና ፫ቱ ሰማዕታት ልጆቿ
በዚችም ዕለት የከበሩ አቡቂርና ዮሐንስ ሦስት ደናግልም ከእናታቸው ከአትናስያ ጋርበሰማዕትነት ሞቱ ። የእሊህም ስማቸው ቴዎድራ ትርጓሜው የእግዚአብሔር ስጦታ ነው ሁለተኛዋ ቴዎፍና ትርጓሜውም የእግዚአብሔር ሃይማኖት ሦስተኛይቱም ቴዎዶክስያ ትርጓሜውም የእግዚአብሔር ምስጋና የእናታቸውም አትናስያ ትርጓሜው ሕይወት የሆነ ነው
::
ይህም የከበረ አቡቂር ከታናሽነቱ በገድል ተጠምዶ የሚኖር መነኰስ ነው የከበረ ዮሐንስ ግን ከንጉሥ ሠራዊት ውስጥ ወታደር ነበር የእነርሱም ሀገራቸው እስክንድርያ ሲሆን የሚኖሩት በአንጾኪያ ነው በንጉሥ ዲዮቅልጥያኖስም ፊት ቁመው ከእሊህ ደናግል ከእናታቸው ከአትናስያም ጋር በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመኑ ። እርሱም ከወዴት እንደሆኑ ጠየቀ ከእስክንድርያ አገር እንደሆኑ በተረዳ ጊዜ ወደዚያ ይወስዷቸው ዘንድ አዘዘ ።
ወደ እስክንድርያ በደረሱ ጊዜ በመኰንኑ ፊት ቁመው በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመኑ መኰንኑም ጽኑዕ ሥቃይን አሠቃያቸው ማሠቃየትንም በደከመ ጊዜ ራሶቻቸውን በሰይፍ እንዲቆርጡ አዘዘ የከበረች አትናስያም ደናግል ልጆቿን በከበረ ስሙ ምስክር ሁነው ከሞቱ ለሰማያዊ ሙሽራ ክርስቶስ እነርሱ ሙሽሮቹ እንደሚሆኑ በማስረዳት ታጸናቸውና ታስታግሣቸው ነበር እንዲሁም የከበረ አቡቂር በከበረች ሐዋርያዊት ቴክላ ላይየደረሰውን መከራ ይገልጥላቸውና ያጸናቸው ነበር ።
ወታደሮችም ለባለ ሰይፍ በማከታተል አንዲቱን ከአንዲቱ በኋላ የሚያቀርቡ ሆኑ ከዚያም እናታቸውን የከበሩ አቡቂርና ዮሐንስንም ቆረጡ መኰንኑም ሥጋቸውን ለአራዊትና ለአዕዋፍ ይጥሉ ዘንድ አዘዘ ምእመናንም ሥጋቸውን በሥውር ወሰዱ በክብርም ገነዙአቸው የመከራውም ዘመን እስቲያልፍ በሣጥን አድርገው ሠወሩአቸው ።
ከዚህም በኋላ ቤተ ክርስቲያን ተሠርቶላቸው ሥጋቸውን በውስጧ አኖሩ ከእርሳቸውም ታላላቅ ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ ። በረከታቸውም ከእኛ ጋር ትኑር ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን አሜን ።
ቅድስት ማርያም እንተ ዕፍረት
በዚችም ቀን ጌታን ሽቱ ለቀባችው ማርያም የዕረፍቷ መታሰቢያ ነው ። ይችም ቅድስት አስቀድማ ኑሮዋን በዝሙት ያሳለፈች ኃጢአተኛ ነበረች ። እርሷም ጐልማሶችን ወደርሷ ትማርካቸው ዘንድ በየራሱ በሆነ ሽልማትና ጌጥ ትሸለም ነበር ።
በአንዲትም ዕለት እንደ ልማድዋ ተሸልማ አጊጣ ሽቱም ተቀብታ ፊቷን በመስታዋት ተመለከተች የጉንጯ ቅላትና ደም ግባቷ የዓይኗም ወገግታና ጥራት ማማሩን አይታ እያደነቀች አንድ ሰዓት ያህል ቆየች ከዚህም በኋላ በጎ ኀሳብ በላይዋ መጣ ሞትንና የዚህን ዓለም ማለፍ አሰበች ።
የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስም ኃጢአተኞችን እንደሚቀበልና ኃጢኣትንም እንደሚአስተሰርይ ሰምታ ገንዘቧን ወስዳ የአልባስጥሮስን ሽቱ ገዝታ በስምዖን ዘለምጽ ቤት ለምሳ ተቀምጦ ሳለ ወደ ጌታችን ሔደች ።
ከእግሩ በታችም ሰግዳ ያንን ሽቱ ቀባችው እግሮቹን በዕንባዋ አጠበችውና በራስዋ ጠጉርወለወለችው ጌታችንም የፍቅርዋን ጽናት አይቶ ኃጢኣቷን በደሏን ተወላት የመንግሥት ወንጌልም በሚሰበክበት ይህን ያደረገችውን እንዲአስቡ አዘዘ ። በረከቷም ከእኛ ጋር ይኑርለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን አሜን ።
የካቲት ፮ ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
፩.ቅድስት ማርያም እንተ ዕፍረት
፪.የዓለም ኁሉ መምሕር ቅዱስ አቡሊዲስ ብዙ መንፈሳዊ ድርሳናትን የደረሰ ሊቀ ዻዻስና ሰማዕት
፫.ቅዱሳን አቡቂርና ዮሐንስ ሰማዕታት
፬.ቅድስት አትናስያና ፫ቱ ሰማዕታት ልጆቿ ቴዎድራ: ቴዎፍናና ቴዎዶክስያ
ወርኀዊ በዓላት
፩.ቅድስት ደብረ ቁስቁዋም
፪.አባታችን አዳምና እናታችን ሔዋን
፫.አባታችን ኖኅና እናታችን ሐይከል
፬.ቅዱስ ኤልያስ ነቢይ
፭.ቅዱስ ባስልዮስ ዘቂሣርያ
፮.ቅዱስ ዮሴፍ አረጋዊ
፯.ቅድስት ሰሎሜ
፰.አባ አርከ ሥሉስ
፱.አባ ጽጌ ድንግል
፲.ቅድስት አርሴማ ድንግል
... አንተ ራሴን ዘይት አልቀባኸኝም ። እርሷ ግን እግሬን ሽቱ ቀባች ። ስለዚህ እልሃለሁ: እጅግ ወዳለችና ብዙ ያለው ኃጢኣቷ ተሰርዮላታል ። ጥቂት ግን የሚሰረይለት ጥቂት ይወዳል ። እርስዋንም:- ኃጢኣትሽ ተሰርዮልሻል አላት ። ከእርሱም ጋር በማዕድ ተቀምጠው የነበሩት በልባቸው:- 'ኃጢኣትን እንኩዋ የሚያስተሰርይ ይህ ማነው' ይሉ ጀመር። ሴቲቱንም:- እምነትሽ አድኖሻል በሰላም ሒጂ አላት ። ሉቃ. 7÷46
@yekidusantarik @Fewus_Menfesawi_Aba_Gebrekidan @EfoyZeOrthodox
Повторяем попытку...
Доступные форматы для скачивания:
Скачать видео
-
Информация по загрузке: